MANDELA ማንዴላ [Poem]

Mandela_D

 

 

 

 

 

ማንዴላ

ማንዴላ ማንዴላ ፤ ማንዴላ ማዲባ

አለቀስኩ ለኔ ፤ ውስጤ ላንተ አነባ

ለግል ሳይሆን ለሕዝብ ፤ ለቡድን ሳይሆን ለሀገር

በሞት መከራ እስር ፤ መቸም ጸንቶ መኖር

የኛ ጥቁር ዕንቁ ፤ የአፍሪካ ሞገሱ

መድኃኒቱ ነበርክ ፤ ለዘር መድሎ ምሱ

ብዙ ጥበብ አለህ ፤ ያንተ የማይረሱ

ለባለ እእምሮ ፤ ካንተ የሚወረሱ

ሊያውቀው የሚገባ ፤ ሁሉም ሰው እንደሱ

በተለይም መሪ ፤ የነከሰ ጥርሱ ፡፡

የማንዴላ ጥበብ ፤ የማንዴላ ትምህርት

ይቅር ማለት ከልብ ፤ ግን ደሞ አለመርሳት፡፡

ተቃርኖ ያላቸውን ፤ እንደ ውኃና ዘይት

ሁለቱን አዋሕደህ ፤ የኖርክበት ሕይዎት

ያስማማህበት ጥበብ ፤ ሁለቱን ባሕርያት

እጅግ ይገርመኛል ፤ የተካንከው ብስለት

የሚቻል የማይመስል ፤ እውን ሆኖ ማየት

በማንዴላ ልብ ውስጥ ፤ ተችሎ ዓየሁት

አዎ ይቅር እላለሁ ፤ ግን አልረሳም ላፍታ

ነበር ያልከው ያኔ ፤ ከእስር ስትፈታ ?

ውለታህን ሳስብ ፤ ላገሬ ያለህ ፍቅር

የእውነት ሰው መሆንህ ፤ ቃልክን የምታከብር

ሐዘን ይሰማኛል ፤ ዐይኔ እንባ በማቅረር፡፡

እንዲያ ሲያስጨንቀው ፤ ሲወርድ ሲወጣ

ኢትዮጵያን እንዳያይ ፤ ለሁለት ተቆርጣ

አንድነቷ እንዳይፈርስ ፤ እንዳትከስር ተሸጣ

ሲመክር ሲያባብል ፤ የሁለቱንም አውራ

እየተማጸነ ፤ አባብሎ እየጠራ

አንተ ጠቅላይ ሚንስትር ፤ አንተ ርእሰ ብሔር

ሆናቹህ አሥተዳድሩ ፤ ተሳስባቹህ በፍቅር

አንድ ሕዝብ የሆነውን ፤ አንድ ማንነት ስር

አታፈራቅቁት ፤ አትለዩት በድንበር

ተራርቆ የማይርቅ ፤ ተነጣጥሎ የማይቀር

ባለ አንድ መልኩን ፤ ያለውን ትስስር

ትዝብት አታትርፉ ፤ በቤተሰብ ፍቅር

ብዙ ነገር አለ ፤ የለም ተውት ይቅር

ለሀገር ጥቅም ሲባል ፤ የማትከፍሉት ነገር

መኖር የለበትም ፤ ምን ተአምር ቢፈጠር

ግድ የለም ባካቹህ ፤ መከፋፈሉ ይቅር

በእርጋታ እስኪ አስቡት ፤ ጠላት ወይስ ወዳጅ ?

ይሄ ነገር ቢሆን ፤ ሲቦርቅ የሚባጅ ?

አንድነት ነው ኃይላችን ፤ ጠላት የሚያሳፍር ፡፡

አላቸው ማንዴላ ፤ ከልምዱ ሲያስተምር

ያውቃልና ሴራው ፤ እንዳለው የማን ሸር

በጦቢያ ጥቅም ላይ ፤ ማን እንደሚቆምር ፡፡

ማዲባ ቀጠለ ፤ መለገሱን ምክር

ሁሉም ኃላፊ ነው ፤ አይምሰላቹህ የሚኖር

ለስማቹህ ኑሩ ፤ እሱ ነው የሚቀር

ታሪክ የሚያስበው ፤ ዘወትር የሚዘከር

ጥሩ በመሥራት ነው ፤ መከበር መፈቀር

ከመቃብር በላይ ፤ ዘለዓለም የሚኖር

ከጥፋት ምን አለ ? ከመጠላት በቀር ?

በራስ ሳይወሰን ፤ ቅስም የሚሰብር የዘር ፡፡

እድለኞች ናቹህ ፤ የዚች ታላቅ ሀገር

የሥልጣኔ ምንጭ ፤ ዋልታ ቋሚ ማገር

ተወላጆች ናቹህ ፤ ዜጎች የአርበኞች ዘር

ምድሯ ያበቀላቹህ ፤ ኢትዮጵያዊ ፍጡር

የተቀደሰ ሕዝብ ፤ የእግዚአብሔር ምድር

የጀግና ሕዝብ ፍሬ ፤ የአፍሪካ ክብር

እንደኔ እንደሌሎች ፤ በውርስ አይደለም

በፍቅሯ ተነድፈን ፤ የተጠመቅነው ስም

በሥጋ አጥንት ፍላጭ ፤ የወጣቹህ በደም ፡፡

ዓይታያቹህም ? ልዕልናው ክብሩ ?

አታውቁትም እንዴ ? ምን ነው አትፎክሩ ?

እኔ እንደማያቹህ ፤ በደም ወይ በትውልድ

ኢትዮጵያዊያን ናቹህ ፤ ባለ ዘንግ ባለ ዘውድ

ጣሊያን ወይ እንግሊዝ ፤ ዓረብ ወይም ሌላ

ምንም አትመስሉኝም ፤ ተልኮ ያለው ከኋላ

እንዲህ ሆኖ እያለ ፤ የማየው እውነታ

ለሀገራቹህ የማይበጅ ፤ ከእድገት የሚገታ

ኋላ የሚፈጥር ፤ ቁርሾና ቅሬታ

ለሰላም የማይበጅ ፤ የሚነሳ ፋታ

ሆድ የሚያሸካክር ፤ የእሳት ላይ ጨዋታ

አሁን የማታውቁት ፤ግን የማታ የማታ

የሚያመሰቃቅል ፤ በጊዜ ቆይታ

የምትመርጡበት ምክንያት ፤ አይገባኝምና

እንዳምን እገደዳለሁ ፤ ሲያቃዠኝ ነው ገና

ካልሆነ ግን እናንተ ፤ ጨርቅ ጥላቹሀል

ከሁለት አንደኛው ፤ በእርግጥ እውን ሆኗል ፡፡

የአሥተዳደር በደል ፤ ችግር አለ ተብሎ

ያንን በደል አድራሽ ፤ መጣል ነው እንጅ ታግሎ

የተገነባችውን ፤ ስንት ዋጋ ተከፍሎ

ልቁረስ አይባልም ፤ ሀገር ተገንጥሎ ፡፡

ማን አለባቹህ አሁን ? ያላቹህ እናንተ

ተቀናቃኝ የለ ፤ ከሄደ ሰነበተ

ተራው የእናንተ ነው ፤ ካለው እስከ ሞተ

በአንድነት በኅብረት ፤ መሥራት ነው በጋራ

በጥሩ አመራር ፤ እንደ ውኃ በጠራ ፡፡

እንደዚህ አርጉ እንጅ ፤ ስለ የደም ካሳ

ሀገር ጓሮ አይደለም ፤ የገበሬ ማሳ

ያም ያም ለብቻየ ፤ እያለ እያገሳ

የሚከፋፈሏት ፤ በእጣ ተቆራርሳ ፡፡

እንዲህ የሆነች ጊዜ ፤ ሀገር መሆኗ ቀርቶ

ብዙ ሽ መንደሮች ፤ ትሆናለች እንቶ ፈንቶ

ሀገር ሀገር የመሆን ፤ ዕድል የምታገኘው

አንተ ትብስ እኔ ፤ በሚል ተቻችለው

በአንድነት በኅብረት ፤ መኖር ስንችል ነው ፡፡

ነገር ግን ቅር ያለው ፤ ልቁረስ ባለ ቁጥር

መቆሚያው የቱ ላይ ፤ እንደሚሆን ድንበር

አስባቹህታል ? ምን እንደሚፈጠር ?

ታች መንደር ይወርዳል ፤ ጎሳንም ተሻግሮ

የየቡድኑ ቅልስ ፤ ትናንሽ የጅ ጓሮ

የሆነች ቁርስራሽ ፤ ልትሆን ነው ምንጣሮ ፡፡

እናም ሀገር ስንል ፤ ሕዝብ ብለን ስንጠራ

ስለ መገነጣጠል ፤ አንችል ልናወራ

አውራ ባለታሪክ ፤ የነጻነት ዘብ አጥር

የአንድነት ተምሳሌት ፤ ያጌጠ በኅብር

የአፓርታይድ ጠላት ፤ የቅኝ ግዛት ጸር

የጥቁር ሕዝብ ፈርጥ ፤ ኩራት ጌጥ ጋሻ ጦር

እንዴት ይሄን ያስባል ? እኮ በምን ተአምር ?

ካከበራቹህኝ ፤ ወንድም ነው ካላቹህ

ልመናዬን ስሙኝ ፤ ጆሮ ሰጥታቹህ

የምስራች ስጡኝ ፤ እሽ እንዳልክ ብላቹህ

እንቢ ካላቹህ ግን ፤ ቃሌን ካልሰማቹህ

ስሜን እንዳትጠሩ ፤ እኔም አልጠራቹህ ፡፡

አንድነት ወዳጣች ፤ ወደ ተቆረሰች

ከታሪኳ ጋራ ፤ ወደተካካደች

ከታላቅነቷ ፤ ወደተዋረደች

ድንቅ አርዓያነቷን ፤ ወርውራ ወደ ጣለች

እግሬን ላላነሣ ፤ ብየ ኢትዮጵያ አለች ፡፡

እለያቹሀለሁ ፤ በእግዚአብሔር ስም ምየ

ወንድም ሕዝብ ናፍቄ ፤ ላልመጣ ዐይኔ  እያየ

ቤቴ እችለዋለሁ ፤ ራሴን አባብየ

ምንም ነገር ቢሆን ፤ እቆርጣለሁ ችየ ፡፡

ይሄ ሁሉ ምልጃ ፤ ያ ሁሉ ተማጽኖ

የኢሳይያስ መለስን ፤ ልብ አሳዝኖ

አርሞ ሊያቀና ፤ ሳይችል ቀረ መክኖ

የእነሱ ጭንቅላት ፤ ክፋትን ጠንጥኖ

ቆርጦ መቷልና ፤ ሊያጠፋ ጨክኖ ፡፡

የታላቁ ሰው ምክር ፤ የሚያነሣ አድኖ

ጭንጫ ላይ ተዘርቶ ፤ ውዱ ቃለ ፋኖ

በቅሎ ሳያፈራ ፤ ቀረ ከንቱ ባክኖ ፡፡

እነሱ የዕለቱን ፤ እሱ የሚያይ አርቆ

እነሱ ላይላዩን ፤ እሱ እጅግ ጠልቆ

እነሱ ያላዩትን ፤ ለእሱ የሚታይ ደምቆ

እሱ ይቅር ባይነት ፤ እነሱ መበቀል

እነሱ የጨለማ ፤ እሱ ደሞ የጸዳል

የሱ ጽናት ለእምነት ፤ የእነሱ ለክህደት

የእሱ አንደበት ለእውነት ፤ የእነሱ ለእብለት

እሱ እልፍ ነው ሲል ፤ እነሱ መቶ ዓመት

እሱ የኔም ነው ሲል ፤ የኢትዮጵያን እሴት

እነሱ የአንድ ዘር ነው ፤ መደምሰስ አለበት

እነሱ ጮርቃ እንጭጭ ፤ እሱ የበሰለ

የሰብእናን ጸጋ ፤ መንፈስ ባማከለ

እነሱ የደኸዩ ፤ እሱ የታደለ

እሱ አህጉራዊ ፤ እነሱ ጎጠኛ

እሱ የቸረ ለጋስ ፤ እነሱ ምቀኛ

እነሱ ጥላቻን ፤ እሱ ሰባኪ ፍቅር

እሱ የማቻቻል ፤ እነሱ የማቃቃር

እንደምን ይግባቡ ፤ ደናቁርት ከምሁር ?

ጦቢያም ተቆረሰች ፤ አካሏ ሁለት ሆነ

ማዲባ አለቀሰ ፤ አረረ በገነ

በኋላ ቆይቶ ፤ ብዙ ከሰነበተ

መለስ ባይገባውም ፤ እንደተሳሳተ

ማዲባን ሊፈትን ፤ እስኪ ይጸናል ቃሉ ?

አልመጣም እንዳለ ፤ ይቀራል ለበዓሉ ?

ብሎ ጥሪ አስላከ ፤ እንዲገኝ መጥቶ

ማንዴላ ሲሰማ ፤ አዘነ ተቆጥቶ

መጥቶም አልተገኘ ፤ ለጠሪው ክብር ሰጥቶ

ምንም እንኳን መርሑ ፤ ቢሆንም ይቅር ማለት

የኢትዮጵያ ነገር ግን ፤ የማይሆን ሆኖበት ፡፡

ማንዴላ ማንዴላ ፤ ማንዴላ ማዲባ

እንደተመኘላት ፤ አንድነት ለሳባ

ያችን ቀን ሲጠብቅ ፤ በደስታ ሊያነባ

እየፈነጠዘ  ፤ ሊያድለን አበባ

አንድ ሆና ሳያያት ፤ ችግሯን አልባ

ሐዘን እንደበላው ፤ በሕልሙ እንደባባ

በእድሜ ተወስኖ ፤ ዐርፎ አፈር ገባ ፡፡

ኅዳር 2006 ዓ.ም.

ሠዓሊ አምሣሉ ገ/ኪዳን አርጋው

[email protected]

Leave a Comment


one + 2 =